ብራና ሚዲያ BRANA MEDIA
361 subscribers
1.3K photos
11 videos
146 files
169 links
Download Telegram
ማስያስ

ዳግም ጥቆማ

#መቅድመ_ነገር

መጽሐፏን ያገኘኋት ከፌስ ቡክ ጥያቄና መልስ ፡ በሽልማት መልክ ነበር ። እንደ አጋጣሚ ሀዋሳ ነበርኩና በአንዲት በጓደኛዬ በኩል መጽሐፉን ተቀብዬ ለመጽሐፉ አዘጋጅ ልባዊ ምስጋናን በማቅረብ መጽሐፉን አንብቤ ከጨረስኩ በኋላ አጠር ያለች ይዘታዊ ዳሰሳ (content review) ለማዘጋጀት ቃል ገብቼ ነበር ። ብዘገይም በቃሌ ተገኝቻለሁ ። ይኸው እነኋችሁ!!!

#የመጽሐፉ_ርዕስና_ዓላማ

ማስያስ ፦ በአረማይክ መሲሕ ፣ በዐረብኛው አልመሲሕ በግሪኩ ደግሞ ማስያስ እያልን የምንጠራውን ሥግው ቃል መድኃኔዓለምን ጥዑመ ስም የያዘ ነው ። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በመጽሐፈ ሰዓታት " ኢየሱስ ክርስቶስ ጥዑመ ስም ለዘይጼውዖ " ያለው ግዘፍ አካል ነስቶ ለአፍ የሚጥም ፣ ለጆሮ ደስ የሚያሰኝ ፣ ለአጋገር የሚመች ፣ ለዓይን የሚስብ ፣ ለንባብ በሚጋብዝ ምጥን ቃል " ማስያስ " በሚለው ስያሜ አግኝቼዋለሁ ።

በመጽሐፉ ሽፋን ገጽ ላይ ጸሐፊው ስለ መጽሐፉ ጠቅላይ ዓላማ (General Objective) " የኦርቶዶክሳዊው ነገረ መለኮት መቅድማዊ ነጥቦች " በማለት መሠረታዊ የሆኑ የነገረ መለኮት ጽንሠ ሃሳቦችን (Conceptual framework of Theology) ሊያስውቅ የሚችል መጽሐፍ እንደሆነ ለመግለጽ ሞክሯል ።

መምህር ብርሃኑ አድማስም ስለ በመጽሐፉ ኆኅት በተገብቶ ዲ/ን ሚኪያስ መጽሐፉን ማስያስ ያለበትን ምክንያት " ክርስቶስ የትንቢት ሁሉ ፍጻሜ ፣ የንባብ ሁሉ ትርጓሜ ፣ የምሳሌያትና የጥላዎች ሁሉ ጥላ አካል ፣ የስብከትና የትምህርት ሁሉ መዳረሻ የአገልግሎት ሁሉ ዓላማ ፣ የጉባኤያት ሁሉ ጉዳይ ፣ የምሥጢራት ሁሉ ማኅተም ፣ የሕይወት ሁሉ እስትንፋስ መሆኑን የሚያምኑ አገልጋዮች ተግባራቸው ሁልጊዜም ይህንኑ እርሱን በምእመናን ልቡና ለማሰደር የሚረዱ ትምህርቶችን ፣ ጽሑፎችን ማዘጋጀትና ማቅረብ ነው ። ዲያቆን ሚኪያስም መጽሐፉን " ማስያስ " ያለበት ምክንያት ይኸው የአገልግሎታችን ሁሉ ማዕከል እና የቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ ምሥጢር እርሱ መሆኑን ለማሳየት ይመስለኛል ። " በማለት የመጽሐፉን ወሳኝ ዓለማ (Critical Objective) ያብራራል ።

#የመጽሐፉ_ይዘት

ይህ በ327 ገጽ ፣ ከ40 በላይ ሀገርኛ ፣ ከ50 በላይ የባሕር ማዶ ማመሳከሪያ ዋቢ መጻሕፍት ፣ በ300 የኅዳግ ማስታወሻዎች(Foot notes) የተሰነደው " ማስያስ " የተሰኘው መጽሐፍ በሰባት ምዕራፎች የተከፈለ ሲሆን

#ምዕራፍ_1 = ኦርቶዶክሳዊ ፍኖተ አእምሮ

- ሃይማኖትን (ክርስትና) የአእምሮ ሕመም (Mental Illness) አድርገው እምነት (Faith) እና አመክንዮ (Reason) በጽንፍ ተቃርኖ ውስጥ ያሉ አድርገው በስህተት ለሚጓዙት የስህተታቸውን ምንነትና የስህተቶቻቸውን መንስኤ ይገልጻል ። ውግንናውን ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ በማድረግ በማስረጃ ይሞግታል ።

- በነገረ መለኮት ትምህርትም ሰፊ ቦታ የሚሰጣቸውን ዕውቀት ፣ አእምሮ ጠባዐይ ፣ አእምሮ መንፈሳዊና ምስጢረ ሥላሴ የተሰኙ ወሳኝ ጉዳዮች ሲያብራራ በተጨማሪም የባሕርየ እግዚአብሔር (Essence of God) አይመረመሬነት በኢ- አውንታዊ ነገረ መለኮት (Negative Theology) የተቃኘውን የአበውና ሊቃውንት ትምህርት ያቀርባል ። እንደ ማጣፈጫ ጨው ከተጠቀሳቸውም መካካል
" በነገረ መለኮት ዕውቀታቸው የተመሰገኑ ሕንዳዊው ሊቀ ጳጳስ ጳውሎስ ማር ጎርጎርዮስ ስለ ልዑል እግዚአብሔር መጻፍ ሲጀምሩ እንዲህ ይላሉ " ስለ እግዚአብሔር ማንነት እንዳስተምር ብጠየቅ ፡ የማስታወሻ ወረቀቶቼን ይዤ ወጥቼ የትምህርቴን ርእስ ተናግሬ ለረዥም ሰዓት ዝም ብዬ ከቆየሁ በኋላ ስላዳመጣችሁኝ አመሠግናለሁ " ብዬ ከመናገርያ ቦታዬ እወርዳለሁ " በማለት ጥልቅ ነገርን ተናግረው ነበር ። " ገጽ 29

#ምዕራፍ_2 = ፍጥረት

- ከላይ በአሚነ እግዚአብሔር የተወጠነው ትምህርት በዚህ ምዕራፍ በአእምሮ ፍጥረተ ዓለም ይጸናል ። በትልቁ ዓለም የሚኖረው ትንሹ ዓለም (Microcosm)፣ ግሩምና ድንቅ የሆነው የሰው ልጅን የፍጥረት ሁሉ ዘውድ የሆነበትን ምክንያት ይዳስሳል ።

- በመቀጠልም በእግዚአብሔር አርአያና መልክ የተፈጠረው የሰው ልጅን ድቀትና ድኅነት በሰፊው ያስቃኛል ።

#ምዕራፍ_3 = የመገለጡ ጥላዎች በብሉይ ኪዳን

- "ሐዲስ ኪዳን ማለት የብሉይ ኪዳን ትርጓሜ ነው " እንዲሉ ወንጌል ሳትሰራ ወንጌልን በጻፉ በብሉይ ኪዳን ወንጌላውያንና በዘመነ አበው ፣ በዘመነ መሣፍንት ፣ በዘመነ ነቢያት ፣ በዘመነ ነገስት " ታሪኮች " ማስያስ "ን እያሳየ ያስደንቀናል ።

- የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መካከለኞች ፣ የሰማያዊ ሙሽራ እናትና ጓደኛ ያስተዋውቀናል ። በተለይን እናቱ በነገረ ድኅነት (Soteriology) ለሰው ልጆች መዳን ስለ አላት ድርሻ ያሳውቀናል ።


#ምዕራፍ_4 = ሥጋዌ

- ቀደም ሲል የሙሽሮቹን እናትና ጓደኛ ያስተዋወቀን ፤ አሁን ደግሞ ሰማያዊው ሙሽራ ማስያስን ያስተዋውቀናል ። የሰርጉ ባለቤት(ማስያስ) ፣ የሰርጉን ዓይነት (ተዋሕዶ) ፣ የሰርጉን ዕለት፣ ሰዓትና ቦታ የሚገልጽ........የሰማያዊ የሰርግ ጥሪ ካርድ ይሰጠናል ።

#ምዕራፍ_5 = ነገረ ቤተ ክርስቲያን

- የሰርጉን የጥሪ ካርድ ይዘን ወደ ሰርግ ቤቱ(ቤተ ክርስቲያን) ይወስደናል ።

#ምዕራፍ_6 = ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓተ አምልኮ

- የሰርጎች ሁሉ ሰርግ በሆነው(ቅዳሴ) ድግስ ያሳትፈናል ።

#ምዕራፍ_7 = ሱታፌ አምላክ
-ከሰርጉ ማዕድ አሳትፎ ከሙሽራው ጋር ያዛምደናል ።


#የመጽሐፉ_ጠቀሜታ

" እስመ ረኪበ ቀጢናት በቀጢናት ፣ ወረኪበ ገዚፋት በገዚፋት ፤ ቀጢን ውእቱ ነገረ መለኮት ወየኀሥሥ ኅሊና ቀጢነ " እንዲሉ አበው ፣ መጽሐፉ ነገረ መለኮታዊ እንደመሆኑ የረቀቀና የመጠቀ ኅሊናን ይሻል። ነገር ግን የመጽሐፉ አዘጋጅ የራቀውን አቅርቦ የረቀቀውን የነገረ መለኮት ሐሳቦች አጉልቶ የታሪክና የሀሳብ ፍሰቱን በጠበቀ አጻጻፍ ውብና ሁሉም አንባቢ ሊረዳው በሚችልና ቀጢነ ኅሊናን በሚሰጥ መልኩ የተዘጋጀ መጽሐፍ ነው ።

ሚከዋ ብዕርህ ትለምልም!!!

መቅድሙ እንዲህ ከሆነ ውስጡ እንዴት ይሆን?

ዲ/ን ዘአማኑኤል ገዛኸኝ
2017/07/11
ሐዋሳ
"ልዩ መንፈሳዊ የኪነ-ጥበብ ዝግጅት"
የአ/አ ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን የሕንጻ እድሳት ኮሚቴ አስተባባሪነት በተዘጋጀው ልዩ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ በአንጋፋ ኦርቶዶክሳውያን የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች (አርቲስቶች) ወግ ÷ግጥም÷ ጭውውት ÷ መዝሙር ዝማሬ ÷ ድራማ ÷ መነባንብ ÷ የአንድ ሰው የመድረክ ተውኔት ÷ እና ሌሎችም ዝግጅቶች ይቀርባሉ፡፡
በዕለቱ ግሩም ኤርምያስ፣አለማየሁ ታደሰ፣ተስፉ ብርሃኔ፣ ትዕግስት ግርማ፣ ሚሊዮን ብርሃኔ፣ መስከረም አበራ ፣ነቢዩ ኤርምያስ እና ሌሎችም ...... ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡

ቀን፡- ነሐሴ 8/2014 ዓ/ም ከቀኑ 7 ሰዓት ጀምሮ
ቦታ:- 4ኪሎ ቅድስት ሥላሴ አዳራሽ
የመግቢያ ዋጋ 300 ብር ብቻ
ለበለጠ መረጃ 0911-117613 , 0913645364 ደውሉ፡፡
ኑ! የልብ መሻትዎን መንፈሳዊ ስራን በመደገፍ ያግኙ!!
መልአከ ብርሃን አድማሱ ጀንበሬ -ሐምሌ 24 1962 ዓ.ም. ዕረፍታቸው ነበር፡፡
እግዚአብሔርን "በትዕዛዝ" ሳይሆን በውዴታ ሁልጊዜ እናመሰግነዋለን። ቅዱስነታቸው አቡነ ሺኖዳ "Life of Thanksgiving" በሚል ርዕስ ያዘጋጁትና "የምስጋና ሕይወት" በሚል ወደ አማርኛ የተተረጎመውን ድንቅ መጽሐፍ ዛሬ ልጋብዛችሁ። መጽሐፉን በእንግሊዝኛም በአማርኛም በሁለት አማራጭ ከታች አስቀምጨዋለሁ። መልካም ንባብ!

@OrthodoxConcepts
@OrthodoxConcepts
@OrthodoxConcepts
ጽዋዔ፡- ታሪካዊ ቁስሎችን ለፖለቲካዊ ውጥረት ከመጠቀም፥ታሪካዊ መድኃኒቶችን ለፖለቲካዊ ውጥረቶች በፈዋሽነት የመጠቀም ጥሪ!!
--------------------------------------------------------------------------
ባለፉት ኀምሳ ዓመታት በሀገራችን የገነገነውና የፖለቲካ ታሪካችን አስኳል የኾነው፥ ርእዮተ ዓለማዊ ታሪክ (Ideological History) ነው፡፡ ርእዮተ ዓለማዊ ታሪክ ደግሞ ታሪክን ለፖለቲካዊ ርእዮተ ዓለም ማስፈጸሚያነት በመሣሪያነት መጠቀም ነው፡፡ ታሪክንና ታሪካዊ ትርክቶችን በማነሣሻ መሣሪያነት ብቻ ስለሚጠቀም፥ ታሪካዊ በደሎች ወይም ቁስሎች ላይ ብቻ ያተኩራል፡፡ በዚህም የተነሣ ሀገራዊ አንድነትንና የሕዝብን አብሮነት በመስበር ርእዮተ ዓለማዊ ፍላጎቶችን የማሳካት ዐቅም ያለው የታሪክ ፈርጅ ነው፡፡ የሀገራችን የግራ ፖለቲከኞቻችን እስከ አኹን ለአገዛዝ እየተጠቀሙበት ይገኛል፡፡ እንደእኛ ብዝኀ ማኅበረስብ ለኾኑ ሀገሮች የማይመረጥ ብቻ ሳይኾን የእልቂት ነዳጅ ኾኖ የሚያገለግል ነው፡፡

በዚህ ረገድ ከታሪክ ትርክቶች የሚወለዱ ማኅበረ ፖለቲካዊ ሕመሞች የበዙብን ሕዝብ ብንኾንም ቅሉ፥ ለገጠሙን እንደዚህ ዓይነት ታሪካዊ እና አኹናዊ ችግሮቻችን ከታሪክ የሚወለዱ ማኅበረ ፖለቲካዊ መድኃኒቶችንም መፈለግ አለብን፡፡ ይኽም ፈዋሽ ታሪክ (Healing History) ነው፡፡ ይኽ የታሪክ ፈለግ የሚያተኩረው ታሪካዊ በደሎችንና ቁስሎችን (Historical Trauma) በማከም ላይ በመኾኑ፥ በሀገረ መንግሥት ግንባታ ውስጥ ማኅበረሰብን እንደሚያጣብቅ ሙጫ ኾኖ የሚያገለግል ነው፡፡

ዘወትር ታሪካዊ ቁስሎችን ለፖለቲካዊ ውጥረት ከመጠቀም ዕብደት በመውጣት፥ ለፖለቲካዊ ውጥረቶቻችን ታሪካዊ መድኃኒቶችንም መጠቀም ያስፈልጋል፡፡ እኔም በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ለማውሳት የፈለኩት ርእሰ ጉዳይ ከቀን ወደ ቀን፤ ከዘመን ወደ ዘመን እየተባባሰ የመጣውንና ሥር እየሰደደ የሚሄደውን የሀገራችንና የቤተ ክርሰቲያናችንን መሠረታዊ ችግሮች ነው፡፡ ዘመንና መስክ ወለድ ችግሮቻችንን በአንጾኪያ እና በአንጾኪያ ቤተ ክርሰቲያን የታሪክ መስታወትነት መመረመር ነው፡፡ የአንጾኪያን ታሪክ መሠረት በማድረግ፥ ያለፈውን ሂደታችንን፣ የደረስንበትን ኅሊናዊና ነበራዊ ሁኔታና የወደፊት አዝማሚያችንን መቃኘት ነው፡፡

የተተነተኑት እያንዳንዱ ታሪካዊ ክሥተትና ኹነት ለዘመናችን ቤተ ክርስቲያን እና ቤተ መንግሥት ትእምርታዊ ውክልና አለው ባይ ነኝ፡፡ ውክልናውም “ምኩራብ የሸመነችውን፥ ቤተ ክርስቲያን ለበሰችው፤” ዓይነትም ይመስለኛል፡፡ እያንዳንዱ ታሪካዊ ክሥተትና ኹነት፥ የአሁናዊ ኹኔታችን መርገፍ ወይም የካርቦን ግልባጭ መሆኑም የሚያጠራጥር አይመስለኝም፡፡ ታሪክ ራሱን ደግሞ የመመልከት ወይም የዚያ ታሪክ አካል የመኾን ያህል ቁርኝት ነው፡፡

መጽሐፉ የቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅን አጠራር መነሻ አድርጎ፥ በአንጻረ አንጾኪያ እና አንጾኪያውያን፥ በራሱ በቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ እንደ ሀገር ለኢትዮጵያውያን፤ እንደሃይማኖት ለኦርቶዶክሳውያን የተላለፈ ጥሪ ነው፡፡ ጥሪው ደግሞ ሀገራዊ መተማመንን መሠረት በማድረግ ከማኅበረ ፖለቲካዊ ቀውስ ሙሻዙር የመውጣት፤ በብሔራዊ መግባባት እና እርቅ ታሪካዊና አሁናዊ ቁርሾን የማከም፤ በማእከላዊነትና በገለልተኝነት ሕዝባዊ በደልን የማበስና የመሻር ነው፡፡
ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን ከብተና፣ ሕዝብን ከመፈናቀል፣ ከስደትና ከእልቂት የመታደግ፤ ሀገራዊ አንድነትንና የሕዝብ አብሮነትን የሚያጸኑ፣ የሃይማኖትና የፖለቲካ ልሂቃንን የማበጃጀት አማናዊ ጥሪ ነው፡፡ መጽሐፉም በየምዕራፎቹ እንዲህ ዓይነቱን ጥሪ ስለሚያዘክር “ጽዋዔ” ተብሏል፡፡ ትርጓሜውም ጥሪ ማለት ነው፡፡

መጽሐፉ የሚያተኩረው በቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ዘመነ ቅስና በነበሩ ማኅበረ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲኮ ሃይማኖታዊ ተዋሥኦ ላይ ቢኾንም፤ በመጠኑ ቅድመ ቅስና እና ድኅረ ቅስና የተከሠቱትን ታሪካዊ ኹነቶችንም ተመልክቷል፡፡ በዚህ ምክንያት ንኡስ ርእሱ የማኅበረ ፖለቲካዊ ቀውስ ምንጭ፣ ተገብሮት፣ ክትያና ምላሽ በቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ዘመነ ክህነት ተብሏል፡፡

ታሪካዊ መቼቱ የተለየ ቢኾንም፥ በዚህ መጽሐፍ በቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ዘመነ ቅስና ስለተከሠቱት ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሃይማኖታዊ ቀውሶች ምንጮች፣ ተገብሮትንና ምላሾችን ስንዳስስ፥ በእነዚያ ቀውሶች ውስጥ የእኛን ታሪካዊና አኹናዊ ቀውሶች ምንጮች፣ ተገብሮትና ምላሾችን መዳሰሳችን ነው፡፡ በዚያን ዘመን ተከሥተው ስለነበሩት የቤተ መንግሥትና ቤተ ክህነት ጋብቻና ፍጥጫ፤ ልዩ ልዩ ነውራት ስንነጋገር፥ ስለ ዘመናችን ቤተ መንግሥትና ቤተ ክህነት ጋብቻና ፍጥጫ፤ ነውራት መነጋገራችን ነው፡፡

በአጭሩ የእኔ ዓላማ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ሦስት ናቸው፡፡ አንደኛው በቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ዘመነ ቅስና የነበሩትን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ ቀውሶችን ጠባይ፣ ምንጭ፣ ተገብሮት (Effect)፣ ክትያና ምላሽ፥ ለእኛ በሚኾን መልኩ መመርመር ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ አንጾኪያ እና የአንጾኪያን ቤተ ክርስቲያን ከመከፋፈልና ከመፈራረስ የታደገበትን ስልተ ነገር ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በሚኾን መልኩ ማመላከት ነው፡፡
ኹለተኛ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ፣ የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ (ፍልቪያኖስ)ና የጊዜው ባሕታውያን አንጾኪያ እና አንጾኪያውያን የገጠማቸውን ብሔራዊ ቀውሶችና መዘዞቻቸውን ለመፍታት የወሰዷቸው ርምጃዎች፥ ለታሪካዊና ወቅታዊ ሕመሞቻችን ድኅነት ሊኾኑ በሚችሉበት ኹኔታ ማጤን ነው፡፡
ሦስተኛ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ለአንጾኪያ እና ለአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲ’ኮ’ ሃይማኖታዊ ስንጥቆች እና ሽንቁሮች መፍትሒ እንዲኾን የአደረጉትን ዕሴታዊና ክሂሎታዊ ብቁነቶቹን፥ የሀገራችን የሃይማኖትና የፖለቲካ ልሂቃን ሊማሩበት በሚችሉት አኳኋን ማመላከት ነው፡፡

መጽሐፉ የተቀነበበት በኵረ አሳብም በአብዛኛው ፖለቲካዊ ትምህርተ መለኮት ሳይኾን፥ ትምህርተ መለኮታዊ ፖለቲካ እንደኾነ ማስታወስ እፈልጋለሁ፡፡ ከዚህ አኳያ መጽሐፉ የሀገራችንንም ኾነ የቤተ ክርስቲያናችንን ማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ወይም ፖለቲኮ ሃይማኖታዊ ኹነቶች በሙሉ አንሥቷል የሚል ድፍረት ባይኖርኝም፥ መነበብ ያለበት ግን በዚሁ ማሕቀፈ እይታና መጽሔተ አእምሮ ነው፡፡
የምንፈልጋቸው የመጽሕፍት አይነቶች ለፈቃደኛ ልቦች
1ኛ ፦ የተዋሕዶ ሃይማኖት መጻሕፍት
2፦ የገድላት እና የድርሣናት መጻሕፍት
3፦የታሪክ የማንኛውም ታሪክ ከሃይማኖት እስከ ግለሰብእ
4፦የባህል መጻሕፍት የማንኛውም ባህል
5፦የሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መጻሕፍት
6፦የፍልስፍና
7፦የስነ ልቡና
8፦ የርዕዮተ ዓለም መጻሕፍት
9፦ በታሪክ ላይ የተተንተራሱ የልብ ወለድ መጻሕፍት እንደ ዝጎራ ያሉ
10፦የማንኛውም ቤተ እምነት አስተምህሮን የያዙ
11፦ የማንኛውም አይነት የመዝገበ ቃላት መጻሕፍት እጅጉን የሚያስፈልጉን እኒህ ናቸው፡፡
12፦ የሥነ ቋንቋ መጻሕፍት
13፦ አስፈላጊ መጽሐፎችን በሶፍት ኮፒም እንቀበላለን፡፡
እነዚህን እና የመሳሰሉትን እንፈልጋለን ለማንበብ ደግሞ ምን ይመረጣል ያገኛችሁት አምጡልን እናንበው
ማሳሰቢያ ፦ በግዕዝ፣ በእግሊዘኛ ፣ በኦሮምኛ፣በትግረኛ፣ በወላይተኛ፣ በሲዳመኛ፣በአገውኛ፣ በሷሌኛ፣እና በመሳሰሉት ቋንቋዎች የተጻፈም እናነባለን፡፡
ምሥራቀ ፀሐይ ጉባኤ ቤት 1000233804626 ቴሌፎን 0962636489
ተቸግረን ያልሠራነውን ጉባኤ ቤት ደልቶን አንሠራውም፡፡
ንባብ ለወሬ

"ንባብ ለህይወት"፣ "ንባብ ለዕውቀት"፣ "ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል"... የሚሉና ሌሎችም ስለ ንባብ የተጠቀሱ ተመሳሳይ አባባሎች አሉ። ማንበብ ግን ለወሬ እንኳ ቢሆን አስፈላጊ ነው። ይህም ከንባብ ጥቅሞች አነስተኛው ደረጃ (minimum of requirement) ነው ማለት ይቻላል። ያነበቡና ሌጣቸውን የሆኑ ሰዎች የሚያነሱት ጨዋታ እንኳ ወዙና ለዛው ለየቅል ነው። የወሬያቸው ጣዕም የእንጨትና የሙዝ ያህል ሆኖ ልዩነቱ በግልፅ ይስተዋላል። ሳሙኤል ቤከር የተባለ ጸሐፊ "ማንበብ የዕውቀት መሠረት ነው። የማያነብ የሚያስበው ያጣል የሚናገረውም ያንሳል" ሲል መናገሩ ምንኛ እውነት ነው..! የማሰላሰል አድማሳችንና ርዕሳችን እንዲሰፋ፣ ንግግራችን ጥልቅ፣ ጥብቅና ማራኪ እንዲሆን ሁነኛው መድኅን ንባብ ነው።

የንባብ ጥም መቁረጫ ምንጮች የሆኑ መጻሕፍት "ንባብ ለህይወት" በሚል ርዕስ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ከዛሬ ሐምሌ 28 እስከ ነሐሴ 2 / 2014 ዓ.ም ድረስ በሚዘልቅ የመጻሕፍት አውደ ርዕይ ይቀርባሉ።

በኤግዚብሽኑ የታሪክ፣ የፍልስፍና፣ የረዥምና አጭር ልብ ወለድ፣ የስነ-ግጥም፣ የሃይማኖት፣ የፖለቲካ፣ የታዋቂ ሰዎች ግለ ታሪክና ሌሎችም መጻሕፍት ለእይታና ለሽያጭ ቀርበዋል። በአውደ ርዕዩ በርካታ መጻሕፍት መደብሮችና ሌሎች ባለ ድርሻ አካላት ስለሚሳተፉበት ከገበያ የጠፉ የቀድሞ መጻሕፍትና በቅርብ ጊዜ ለሕዝብ የተዋወቁ አዳዲስ መጻሕፍትም ይገኛሉ። በ2012 ዓ.ም እና በያዝነው 2014 ዓ.ም ለሕትመት ያበቃኋቸው "ምልሰት" እንዲሁም "የሳንኮፋ ሰንኮፍ እና ሌሎች" የተሠኙ መጻሕፍቶቼ በኤግዚብሽኑ ይገኛሉ።

አንባቢያን አውደ ርዕዩን ጎብኙ... መጻሕፍትን ግዙ... አንብቡ...!
የመጽሐፉ ርዕስ፦ የነገረ መለኮት መግቢያ
የመጽሐፉ አዘጋጅ፦ መምህር ግርማ ባቱ
የመጽሐፉ የገጽ ብዛት፦ 290
የመጽሐፉ ዋጋ፦ 170 ብር
የኅትመት ዘመን፦ 2012 ዓ.ም
መጽሐፉ በአራት ምዕራፎች የተዘጋጀ ነው። የመጽሐፉን መቅድም ያዘጋጀው በመጻሕፍት መቅድም እና መግቢያ ላይ የማናጣው መምህር ብርሃኑ አድማስ ነው። መምህር ብርሃኑ በመቅድሙ ላይ "መልካም ነገር እነሆ" በሚል ርእስ በማቴዎስ ወንጌል 19፥16-17 ያለውን ኃይለ ቃል በማንሳት ስለመልካምነት ካብራራ በኋላ የመጽሐፉን መልካምነት እንዲህ ሲል ያውጃል፦ "የመምህር ግርማ መጽሐፍ፣ በምንጩ፣ በትምህርቱና በምሥጢሩ መልካምነቱ እንደተጠበቀ ሆኖ በአቀራረቡ ደግሞ በዘመናችን ያለውን የጥናት ወይም የምርምር መንገድ የተጠቀመ መሆኑን መርሣት ተገቢ አይደለም።"
የመጽሐፉ መግቢያ የተዘጋጀው የመጽሐፉ ጸሐፊ በሆኑት በመምህር ግርማ ባቱ ነው። መምህር ግርማ በመግቢያቸው ነገረ መለኮት የምሥራቅ እና የምዕራብ እየተባለ የሚከፈል መሆኑን እና ከምሥራቁ ወገን እኛን ኦሪየንታሎችን ጨምሮ እነ ግሪክ፥ ሩሲያ እና የመሳሰሉት ሲገኙበት በምእራቡ ወገን የሮማ ካቶሊክና እና ልጇ ፕሮቴስታንት እንደሚገኙ ይነግሩናል። እንዲሁም የእኛን የምሥራቁን ነገረ መለኮት "ተማህልሎአዊ" የሚል ሀገራዊ ሥያሜ ይሰጡታል። ይሄም Mystical, Apophatic, Negative Theology የሚባሉት የሚተካ ነው። ተማህልሎአዊ መንፈሳዊነትን እና ምሥጢራዊነትን አስተባብሮ የያዘ መገለጫ ነው። በምናውቀው ምሥጢራዊ እውቀት እና በምንኖረው መንፈሳዊ ሕይወት መካከል ምንም የተሠመረ ድንበር የለም።
ይሄም በሊቁ Viladmir Lossky አገላለጥ ሲገለጥ "The Eastern Tradition has never made a sharp distinction between mysticism and theology; between personal experience of the divine mysteries and the dogma affirmed by the Church."
ተማህልሎአዊ ያሰኘውም እንዲህ ዓይነቱ የነገረ መለኮት ሕይወት ነው። መምህር ግርማ እንዲህ ዓይነቱን ነገረ መለኮት ከምዕራቡ ክርስትና የተሠወረ ነው በማለት በምሥራቅ እና በምዕራቡ የክርስትና ዓለም ያለውን የነገረ መለኮት አቀራረብ(Theological Approach ) ልዩነት በመጠኑ ይነግሩናል።
የኦርቶዶክሳዊው ነገረ መለኮት(Mystical Theology) ትሑት፥ ተማህልሎአዊ፥ አሉታዊ(Negative)፥ መጽሐፍ ቅዱሳዊ፥ ከጥንታውያን የቤተክርስቲያን አባቶች አስተምህሮ፥ ሕይወትና ጽሑፎቻቸው ጋር የተመሳከረ (patristic) እና ባለ ብዙ ምንጭ ነው። በማለት የምሥራቁን የነገረ መለኮት የአቀራረብና የአረዳድ ምሥጢራዊነት ይገልጹታል።
ይሄን Kallistos Ware እንዲህ ይገልጹታል "Orthodox Theology is less systematic and more Mystical in its approach"
የምዕራቡ የነገረ መለኮት አቀራረብ ደግሞ ሳይንሳዊ፥ ፍልስፍና መር፥ አዎንታዊ(cathaphatic) ማለትም ከሰው አቅም በላይ የሆኑትን መለኮታዊ ምሥጢራት ጭምር ደፍሮ የሚበይን እና በአጥኚው ግለሰብና በሚጠናው እውነት መካከል የአጥኚና የተጠኚ ግንኙነት(subject - object relationship) የፈጠረ ነው።
በማለት በሁለቱ የነገረ መለኮት አቀራረቦች መካከል ያለውን ልዩነት ይነግሩንና ከሁለቱ መካከል ኦርቶዶክሳዊ የሆነውንና መጽሐፉም የቀረበበትን ተማህልሎአዊውን ነገረ መለኮት በመግቢያችው በደንብ ያስተዋውቁናል።
የመጽሐፉ የመጀመርያው ምዕራፍ ተማህልሎአዊ ነገረ መለኮት(Mystical Theology) በሚል ርዕስ ይጀምራል። በዚህ ርዕስ ሥር ልክ እንደ ኦሪቱ የዘፍጥረት መጽሐፍ ስለሀለዎተ እግዚአብሔር (Existence of God) በመናገር ይጀምራል።
"ክርስቲያናዊ ነገረ መለኮት በሀልዎተ እግዚአብሔር ላይ ባለ ፍጹም እምነት ይጀምራል" በማለት በኦርቶዶክሳዊው በነገረ መለኮት ትምህርት ሀለዎተ እግዚአብሔር የሚሰጠውን ቦታ ይዳስሳል። እንዲሁም በሀልዎተ-እግዚአብሔር ዙሪያ ያሉት አመለካከቶች ማለትም አማኒነት(Theism) ኢ-አማኒነት(Atheism) እና ኢ-ታዋቂነት(Agnosticism) በመጠኑ ይዳስሳል። በተጨማሪ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ "የነገረ መለኮት አረዳድ እና ብያኔ በዘመናችን"ና "ዕውቀት እና ነጽሮተ እግዚአብሔር" የሚሉ ሁለት ንዑሳን ርዕሶች ተዳሰውበታል።
በምዕራፍ ሁለት የነገረ መለኮት ምንጮች(Sources of Theology) በሚል ርዕስ እግዚአብሔር በተለያየ መልክ እና ጎዳና እራሱን ለሰው ልጆች በአቅማቸው ልክ የገለጠላቸውን መገለጦችን የነገረ መለኮት ምንጮች አድርገን የምንጠቀም መሆናችንን የሚዳስስ ምዕራፍ ነው። በዚህ ምዕራፍ የእግዚአብሔር መገለጥን (Revelation) በሁለት መከፈላቸውን እነርሱም አጠቃላይ መገለጥ(General Revelation) እና ልዩ መገለጥ(Special Revelation) እንደሚሰኙ ይገልጣል። አጠቃላይ መገለጥ(General Revelation) የሚባሉትን፦ የግዑዙ ዓለም ተፈጥሮ(physical Nature)፥ የሰው ተፈጥሮ(Human Nature) እና ታሪክ(History) እንዲሁም ልዩ መገለጥ(Special Revelation) ተዳሰዋልን። በተጨማሪም የነገረ መለኮት ምንጮች የሆኑትን ትውፊትን(Tradition) መጽሐፍ ቅዱስ(The Holy scripture) የአባቶች ትምህርት ፥ ዓለም አቀፍ ጉባኤያት ውሳኔዎች፥ ሥርዓተ አምልኮ(Liturgy), ፥ ምሥጢራት(sacraments) የሚባሉት የኦርቶዶክሳዊ ነገረ መለኮት ምንጮች በስፋት ታይተዋል።
ምዕራፍ ሦስት በመጽሐፉ ሰፊውን ሥፍራ የያዘ ምዕራፍ ነው። ኦርቶዶክሳዊ ነገረ ሰብእ በሚል ርዕስ ሰው በኦርቶዶክሳዊው ነገረ መለኮት እንዴት ይታያል የሚለውን እያነሳ በተቀራኒው ያሉትን ፍልስፍናዊ እና ሳይንሳዊ እይታዎችን በምሥራቃዊ የነገረ መለኮት መነጽርነት ይተቻቸዋል። በተጨማሪም ለኦርቶዶክሳዊው ነገረ ሰብእ(Orthodox Anthropology) መሠረት የሆነውን የእግዚአብሔር አርያና አምሳል የሚሉ አሳቦችን ሕሊና አበውን በመጠቀም ኦርቶዶክሳዊው ነገረ መለኮት የትክክለኛው ሰብአዊ ክብር ምንጭ መሆኑን ይነግረናል። እንዲሁም ነገረ ሰብእ በነገረ ክርስቶስ(Christological Anthropology), ፥ ወላዲተ አምላክና ነገረ ሰብእ(Theotokos and Anthropology)ና ምሥጢራተ ቤተክርስቲያን እና ነገረ ሰብእ በሚሉ ርዕሶች አማካኝነት ከጥንተ ተፈጥሮ ጀምሮ የእግዚአብሔርን አርአያና አምሳል ይዞ ከመፈጠር፥ በእመቤታችን ምክንያትነት በምሥጢረ ሥጋዌ እንዲሁም በምሥጢረ ጥምቀት እና ቁርባን፥ በቤተክርስቲያን ውስጥ ያለ ፍጹም ማንነትን መሠረት በማድረግ ኦርቶዶክሳዊው ነገረ ሰብእ በስፋት እና በጥልቀት ተዳሷል።
የመጨረሻው ምዕራፍ ማኅበራዊ- አከባበያዊ ነገረ መለኮት(socio-Ecological Theology) በሚል ርዕስ የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር ጋር ባለ ምሥጢራዊ ኅብረት እንደጠበቀ ከሰው ጋር እና ከተቀረው ፍጥረት ጋር እንዴት ያለ ጤናማ ግንኙነት ሊኖረው እንደሚገባ "ሰው ከሰው" እና ነገረ መለኮትና ሥነ ምሕዳር በሚሉ ንዑሳን ርእሶች አማካኝነት ይዳስሳል። ለዚህ ጤናማ ማኅበራዊ እና ሥነ ምኅዳራዊ ግንኙነት የቤተክርስቲያን አስተምህሮ ምን ያህል ለሀገር አስተዋጽኦ እንዳደረገና የጋራ የሆነ አገራዊ ስሜትን ከመፍጠር እና በየገዳማቱ ያሉትን የተፈጥሮ ጥበቃዋን እያነሳ የቤተክርስቲያኒቱ ባለውለታነት አሰምቶ
ይናገራል።
በአጠቃላይ በዚህ መጽሐፍ የምሥራቁ ኦርቶዶክሳዊ ነገረ መለኮት ምን መልክ እንዳለው፥ በእግዚአብሔር መገለጥ ላይ የተመሠረቱት ምንጮቹንና የምንጮቹ ነገረ መለኮታዊ አረዳድ፥ ሰው ምንድነው? የሚለውን ጥያቄ መሠረት ያደረገውና በነገረ መለኮት ሰፊ ሽፋን የሚሰጠውን ኦርቶዶክሳዊ ነገረ ሰብእን በማስረዳትና በመተንተን የሰው ልጆች ክብራቸውን አውቀው እግዚአብሔርን ወደ መምሰል(Theosis) የክርስትና ጉዞ እንዲያቀኑ የሚያደርግ ነው። እንዲሁም እግዚአብሔርን በመምሰል ሂደት ውስጥ የምናገኛቸውን ሰው እና ሌሎች ፍጥረታትን እንዴት ባለ አኳኋን መመልከት እንዳለብን ባጠቃላይ ከእግዚአብሔር እና የእርሱ ከሆኑት ፍጥረታት ጋር ምሥጢራዊ እና መንፈሳዊ ኅብረታዊ ግንኙነት እንዲኖረን የሚያግዝ የሚያስረዳ እና የሚራዳ መጽሐፍ ነው።
ለመምህራችን እግዚአብሔር ይስጥልን። ከእጅ ቁርጥማት ከደረት ውጋት ይሰውርዎት! ወርቃማ ብዕርዎት ትለምልም! ለመጽሐፍ ቀጠሮ ያብቃን!!!

መጽሐፉን ያንብቡ ያስነብቡ!!

እውነተኛ የነገረ መለኮት መግቢያ በሩ ይሄ ነው!