ኢትዮጵያዊ ወጎች #Ethiopian
1.5K subscribers
314 photos
3 videos
18 files
50 links
Download Telegram
#የማንቂያ ደውል ይሁነን!

"ሳል፣ ትኩሳት፣ ለመተንፈስ መቸገርና የራስ ህመም የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ምልክቶች ቢሆኑም አንዳንድ ሰዎች ምንም አይነት ምልክት ሳያሳዩ #ፖዘቲቭ ሊሆኑና ወደ ሌሎች ሰዎች የማስተላለፍ ዕድል ሊኖራቸዉ ስለሚችል ምልክቶች ታዩም አልታዩ የሚደረጉ መሰረታዊ የጥንቃቄ መመሪያዎችን መተግበር አማራጭ የሌለዉ ተግባር ነው" - አቶ አለማየሁ አልዬ (የሀላባ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ)

#Stayhome
#staysafe
If You cannot do great things, Do small things in a Great way.

Napoleon Hill

Have a great day
#StaySafe
ድሮ ተማሪዎች ሆነን፡ ከሚያዝናኑኝ ነገሮች አንዱ ቅጣታችን
ነበር።
" አየለ! "
" አቤት ቲቸር "
" ና ውጣ! "
" ምን አጠፋው? ቲቸርዬ "
" እሁድ በሰፈራችሁ ሳልፍ በሴት ድምጽ ' ጊሽጣው ' ብለኸኛል
"
" ኧረ....እኔ "......
ቲቸር ማሩ ባገኙት ነገር ነው የሚማቱት። ጊዜ አይሰጡም!
ቷቷ ጧጧ ግው ጭው ድው...ካደረጉ በኋላ አራግፈን ስንነሳ ለኛ
ብለው እየመከሩን እንደሆነ ይነግሩናል።
አየለ ዘለግ ስለሚል በዱላ ነው የሚስተናገደው
ዧዧ...ጀርባውን
እውነቱን ለመናገር አየለ እንዳይገረፍ ጸሎታችን ነው
በተዠለጠ ቁጥር፡ ከጃኬቱ የሚነሳው አቧራ ተዉት!
" አንት ጅምር አህያ! " እያንከባለሉ...አባሱት ጭራሽ!
°°°°°°°°°°
አንድ ቀን የቲቸር ምስራቅ ወንበር ላይ የሞተ እንቁራሪት
ያስቀመጠውን መጠቆም ስላልቻልን በመደዳ እንድንገረፍ
መምህርቷ ሃሳብ አቀረቡ
በ75 ተቃውሞና በሳቸው ድጋፍ ጸደቀ!
" ማነው ስምህ? "
" ፍቅሬ "
" መምህር ሙላቱ ጋር ሂድና 4ኛ C ዎችን ልገርፍ ስለሆነ
ከቢልልኝ ጋር ሆናችሁ አግዙኝ ብላችኋለች ምስራቅ "
በላቸው!......እኔንኮነው የሚልኩት!
እሺ ብዬ ሄድኩ
" ቲቸር! " አልኳቸው መምህር ሙላቱን
" ምንድነው? "
" አይ፡ ቲቸር ምስራቅን እንዲያግዟቸው ነው "
" ምን እየሰራች? !
" ሊገርፉን ስለሆነ አግዙኝ ብለዋል "
ቲቸር ሙላቱ ሳቅ አፈናቸው
" ጥሩ!..... አለንጋ ብቻ ነው ያላት ማቴሪያል? "
.....ሙያ አደረጉትንዴ?......
" ለማንኛውም ያንን ጉማሬ አለንጋ ያዝ "
አሉና ትላልቅ አጣና ይዘው ተከተሉኝ።
አረማመዳችንና የተሸከምነውን ለሚያይ ገራፊና ተገራፊ
አንመስልም።
ለክፍላችን መገረፊያ የተሸከምኩትን ጭነት ክፍላችን አመጣነው።
ስንደርስ ቢልልኝ የተባለው ጥበቃ ቀድሞ ደርሶ፡ አዳሜን
ሰባብሯታል።
ክፍላችን የሰልስት ለቅሶ አይነት በስሱ ሲለቀስባት ሰማሁ፡፡
ለካ ዱላው ሲበዛ እኔ በሌለሁበት፡ በኔ ላይ ተደፍድፏል!
" ሙላቱ እንዳትለቀው! እራሱ ነው! ያዝ! "
.......ተበላሸሽ ፍቅርሻ!..........
እንደሮኬት ተወነጨፍኩ!
ዞር ስል ቲቸር ሙላቱ በንዴት አጣናውን እንደያዙ ያባርሩኛል
" ሙላቱ አጣናውን ጣል! " ይላል ቢልልኝ በጩኸት
ቲቸር ሙላቱ ገዋናቸው በንፋስ ወደኋላ እየተወጠረ ዞሬ ሳያቸው
ሳቄ መጣ።
" ሌባ ! ሌባ! ሌባ! ".....ሲሉ ደነገጥኩ!
ጥበቃዎቹ ከያሉበት እንደ ግሪሳ ከበው እላዬ ላይ!....
" አለንጋ ከአስተማሪ ይሰረቃል? "
እጄ ላይ ነበር!
Fikre Z Bhere Ethiopia

#ሠናይ ውሎ ውብ ቅዳሜ ተመኘንላችሁ

#StaySafe
የፖለቲካ ቋንቋችን
(በእውቀቱ ስዩም)
እጄን በሳሙና ከመታጠብ በተረፈኝ ጊዜ ለንጀራ የሚሆን ስራ
እሰራለሁ፤ ማታ ማታ ደግሞ አፌ ላይ ነጭ ሽንኩርት፤ ትከሻየ ላይ
ነጭ ጋቢ ጣል አድርጌ ዩቲውብ ላይ እጣዳለሁ፤
ከፊልሙም ከዘፈኑም ቀማምሼ ያገሬን ቃለመጠይቅ ወይም
ውይይት መመልከት እጀምራለሁ:: አልናደድም፤ አላዝንም፤
እንቅልፍ ደርሶ ከነዚህ ስሜቶች ይገላግለኛል : :
አይበልብንና በእለት ተእለት ውሉዋችን በፖለቲካ አማርኛ
የምንግባባ ቢሆን ህይወት እንዴት እጅ እጅ ይል ነበር? ሳስበው
ራሱ ዘገነነኝ! ነገሩን በንፅፅር ለማየት የሚከተለውን ከፍቅር
እስከመቃብር የተቀነጨበ ውብ ስነፅሁፍ አንብቡልኝ፤
“ ሰብለ ወንጌል የገብሬን አንዲር እንዲህ በሩቁ በሰማች መጠን
ያፏ ምሬት እየጣፈጠ፤ ጠቅላላ ስሜቷ ካዘን ወደ ደስታ
እየተለወጠ ሄደች፤ የእንባ ጎርፍ ያበላሸው ፊቷ እንደገና ውበትና
ደም ግባት ትንሽ በትንሽ መቀባት ጀመረ፤”
( ፍቅር እስከ መቃብር፤ ሀዲስ አለማየሁ ገፅ 96)
ይሄንን አንቀፅ አንድ የዘመናችን ፖለቲከኛ ቢፅፈው እንዲህ
ሊያደርገው ይችላል፤
“ በአማራ ክልል ፤ ምስራቅ ጎጃም ዞን ነዋሪ የሆነችው ፤ሰብለ
ወንጌል ከአርብቶ አደርነቱ ጎንለጎን ባህላዊ የሙዚቃ መሳርያ
በመጫወት ህብረተሰቡን የሚያገለግለውን የገብሬን ዋሽንት
ከፍተኛ ትኩረት መከታተል ጀመረች፤ በከባድ ቀውስ ውስጥ
ተዘፍቆ የቆየው ገፅታዋ ተሻሻለ ፤ ቀደም ብሎ የነበረው እና ዛሬ
ድረስ እየተንከባለለ የመጣው ሀዘኗ ባስቸኳይ ተቀረፈ! መስቀልኛ
መንገድ ላይ የነበረ ውበቷ ቀስ በቀስ ወደ ትክክለኛ መስመር
መመለስ ጀመረ! ለረጅም ጊዜ ተራርቀው የነበሩት ፊቷና ደም
ግባቷ ተቀራርበው መነጋገር ጀመሩ! "
( የፀጥታ ችግር እስከ መቃብር፤ አንቀፅ 96)

#ሠናይ ውሎ
#Staysafe
የሁለተኛ ክፍል በሮች
°°°°°°°°°°°°°°°°°°°°
" ይሄ ክፍል መረጨት አለበት!....ሰላቢ በዛ! "
" ምነው መምህር? "
" ለሽንት ወጥቼ ስመለስ ጭር ይልብኛል "
ከዋናው መንገድ የሚዋሰነው የክፍላችን ግድግዳ ቆርቆሮ ነበር።
ከኋላ ጥግ ያለችውን ቆርቆሮ፡ ሚስማሮቿን አርቆ አሳቢ
ፎራፊዎች አላልተውት በ shortcut ይፎርፋሉ!
" 4 X 3 = ? ስለው ያለቀሰው ልጅ የት ሄደ? "
" አላየነውም ቲቸር "
" ቅድም ሲነፋረቅኮ ቁጥሮቹ የሞቱበት መስሎኝ "
እንስቃለን
" አስታወሳችሁት? "
" አዎ "
" አሁን ወጣ ከማለቴ፡ የት ሄደ? "
" አላየነውም "
" ተባይ ሁላ!! "
ያሬዶ እሳቸው ወጣ ሲሉ፡ ሚስማር የሚያላላ ኮሚቴ ተዋቅሮለት፡
ሾልኮ ሄዷል!
*
በጣም የሚደነግጡት ግን መንገደኞች ነበሩ!
" ሰሃሊትነ!..." አሉ አንዲት ጠና ያሉ ሴት፡ ማሞ ድንገት
ፍልቅ ሲልባቸው ከክፍሉ።
" ምነው ልጄ? በስኳሬ ላይ? ".......
ማሞ እድለ ቢስ ነበር። የደረጃ ተማሪ ቢሆንም፡ አባቱ ግን
ውጤቱን አይቀበሉትም ነበር
ሰኔ ሰላሳ ማሞ ሲገረፍ፡-
" እንዴት 2 ብቻ ታመጣለህ!? "....እየዠለጡ
" አባዬ ላስረዳህ ቆይ! "
" መምህርህን አስረዳ! "
" ኧረ አባዬ! "
" ዝምበል! የአጉኔ ልጅ 71 ሲያመጣ አንተ ሁለት? "
" ኧረ ደረጃችን ነው አባዬ? "
" የምን ደረጃ? "
" እኔ ሁለተኛ ነው የወጣሁትኮ! "
" ምን ያንቀዠቅዥሃል? ረጋ ብትል 71ዱን ትዘግን ነበር! "
**
አንድ ቀን ግን ያቺ መፎረፊያ ተባነነች
ደምሴን ለመስወጣት በተደረገው ኦፕሬሽን የላሉት ሚስማሮች
ወልቀው ጠፉ!..ዝም ብለን አስደገፍናት!
ቲቸር ግስላ ዳኒን ለመኮርኮም ሲንጠራሩ፡ የውጪው ንፋስ
በሃይል ገፍትሯት አናታቸው ላይ ተኛች!
...ሙሴ የተማራችሁ አስታውሱ!.....
መንገደኞች በተከፈተው በኩል እያሰገጉ ቲቸርን በንቀት እያዩ
" አስተማሪም ይፎርፋል?? "

Fikre Z Bhere Ethiopia

#ሠናይ ቀን ከሙሉ ጤና ጋር ተመኘንላችሁ
#Staysafe
የሙት ሐሳብ ጣዕም(ልዑል ኃይሌ)
'የአባ ሎራ' ሐሳብ
የሮሚዮና ዡሊየት ጣፋጭ ህልም ፈቺ፤
ከክፉ ዕድል አዳኝ
ያ'ሰት ሞት ነሽ አንቺ፤
ድልድይ ነሽ ለሮሚዮ
በፍርደ ገምድል ፍርድ መንገዱ ለጠፋው፤
ይኸው ዕድሜ ላንቺ!...
በቁሙ ያጣውን
የታረደ ፍቅሩን በሞት ፅዋ ሰፋው፤
.
እኔም ባንቺ መላ
ብሞት መች ሊቆጨኝ ደጋግመሽ ግደይኝ፤
የሞት ሐሳብ ሆነሽ
ልትጎጂኝ ተነሺ ዡልየቴ ላይ ጣዪኝ፤
.
እኔም እጓዛለሁ!
አንቺ ባቀናሽው የሙት ቃል ጎዳና፤
ካንቺ ሐሳብ ባሻገር
ቆማ ምትጠብቀኝ ሙት ሴት አለችና፤
.
ግንቦት 12, 2012 ዓ.ም.
#StaySafe
መርዶ
[በዕውቀቱ ሥዩም]
____________
ተምትም አሻግሬ የሚባል ጓደኛ ነበረኝ ። አይ ተምትም አሻግሬ !
ባሰብሁት ቁጥር ሳቄ ዝም ብሎ ይመጣል ።
ተምትም ንግግር በማስረዘም ተወዳዳሪ የለውም ። ለምሳሌ
አብረን አምሸተን ስንለያይ እኔ ''ቻው!'' እለዋለሁ። እሱ ግን
'' ....ደህና አምሸተህ ሌሊቱን በሰላም ታሳልፍ ዘንድ
እመኝልሃለሁ!'' ይላል ።
ቁርስ ልንበላ ስናዝዝ '' ቋንጣ ፍርፍር!'' ብሎ እንዳይገላገል ''
''እስቲ እባክሽ የኔ እመቤት ፣ ሽንኩርት ሳይታይ ፣አንድ ጥሩ የሆነ
ከቋንጣ የተሰራ የእንጀራ ና የልዩ ልዩ ነገሮች ፍርፍር አምጭልኝ
....'' ይላል ።
ተምትም እና እኔ አንድ ቀን የጓደኛችን የደመቀ ባይከዳኝን
ወንድም ሞት ሰማን። መርዶውን ለመናገር የታጨን ሁለታችን
ነበር። ''እኔ ቀስ ብዬ ብነግረው ይሻላል !....አንተ ታስረዝማለህ!''
አልኩት። እሱ ግን የንግግር ሱስ ስላለበት ተቃወመኝ።
''ምን ነካህ!....መርዶ እንዲህ ቀላል ነገር ነውንዴ ?....እኔ ነኝ
በዘዴ ልነግረው የሚገባ ....ይልቅ ራሱን የሳተ እንደሁ አንተ
ትደግፈዋለህ!'' አለኝ ።
ከብዙ ጭቅጭቅ በኃላ እሱ አሸነፈኝ ። በማግስቱ ሌሊት ወደ
ደመቀ ቤት ስንሄድ ''አደራ እንግዲህ እንዳታንዛዛው....ወንድምህ
በመኪና አደጋ ስላረፈ ርምህን አውጣ ! ማለት ብቻ ነው'' አልኩት
።።
እሺ ብሎኝ ገባን።
ደመቀ ከእንቅልፋ ተነስቶ በር ከፈተልን በኃላ {ምነው በደህና?}
አለን ። ምልክት ሳሳየው ተምትም ንግግሩን ለቀቀው ''ውድ
የተከበርከው ወንድማችን ደመቀ ባይከዳኝ....ወንድምህ ከሁለት
ቀናት በፊት እናቱን ለመጠየቅ መኪናውን እየነዳ መውጣቱን
ሳታስታውስ የምትቀር አይመስለኝም....ያን ቀን ከሌሎች ቀን
የከበደ ቀን ነበር ....ሰማዩ ርጉዝ አህያ መስሏል ።ወንድምህ
ምነው ዛሬ ቀፈፈኝ እያለ ለራሱ በመናገር መኪናውን በአባይ
ጎዳና ማሾር ጀመረ ...ጸጥ ያለ መንገድ ነበረ ...ምነው የሆነ
መልአክ ተመለስ ብሎ ሹክ ባለው !...ዋ! .....ጎደሎ ቀን ! ዋ
የተሰበረ ዕድል ....ምንኛ ያሳዝናል! ....በአባይ ሽለቆ ውስጥ
ሲገባ የመኪናውን ፍጥነት አልቀነሰም ፤ እናም ወደ ግራ
እዞራለሁ ሲል መኪናው እንደ ኳስ ነጠረች !... ከዚያም ሙሽራ
ሙሽሪትን እንደሚስም ሁሉ መኪናዋ ባቅራቢያው ካለ ቋጥኝ ጋር
ተሳሳመች....ግው! ጓ!
ወንድምህ ! ያ! ቅን ወንድምህ ከዚህ የጨቀየ ዓለም ወደ
ብርሃናዊውና የማይከስመው ዓለም የተሸጋገረው በዚህ ጊዜ
ነው !'' አለና ትንፋሹን ዋጠ።
ደመቀ ግን '' አልገባኝም !'' ብሎ ወደ እኔ ተመለከተ ።
'' ወንድምህ አርፏል !'' አልኩት በፍጥነት ። እሱም በፍጥነት
ወደቀ ።
#stayHome
#Staysafe
ʟօʋɛʀs ɛʍքɨʀɛ :
"እኔ_ደግሞ …."
(አሌክስ አብርሃም)

ምንድነው እንደዚህ - ፊቴን በብረሃን
ከንፈሬን በውብ ሳቅ - የሚያጥለቀልቀው፣
ምንድነው ከልቤ - ኮለል ያለ ሰላም - በጧት የሚፈልቀው?።
እያልኩ አስባለሁ ……

እኔ ደግሞ …..
ምንድነው ሰው ሁሉ- ነጫጭ ክንፍ አብቅሎ - መ,ላክ የመሰለው፣
ምንስ ነው ሰማዩ - እንዲህ ተጠቅልሎ -
በጀ የምይዘው - መሃረም ያከለው።

ኧረ ምን ታምር ነው - መሬት መዞር ትታ - በፎይታ ያቆማት፣
ምንድነው ጨረቃን - ከሰማይ አወርዶ - ምድር -ያሳረፋት?።
እያልኩ አስባለሁ

እኔ ደግሞ …..
የጠሉኝን ሁሉ - ድንገት የመውደዴ፣
መሬቱን ለቅቄ - ባየር ላይ መንጎዴ።

ምንድነው ሚስጥሩ-ቆይ ውስጤን ምን ነካው፣
አለም እንዲህ ጠቦ - በርምጃ ሚለካው።

ውቂያኖስ በፍኘ - ተጨልፎ የሚደርቅ፣
ተራራው በክንዴ - ተጎሽሞ ሚደቅ።

ማነው በመንገዴ - ሳልፍ እልል የሚለው አበባ ነስንሶ፣
ማነው ግማሽ ልቤን - ሸርፎ የወሰደው -በትልቁ ቆርሶ?።
ኧረ ምን ታምር ነው ?
እያልኩ አስባለሁ

እኔ ደግሞ …..
መንገዳኛው ሁሉ - የተከፋ ፊቱን -
በማን ተነጠቀ፣
ከጨፍጋጋ ፊቶች - የዚህ አይነት ብርሃን - እንዴት ፈነጠቀ።

ሚሊየን ህፃናት - ቀልብ በሚነሳ -
ስርቅርቅ ድምፃቸው፣
የት ቢዘምሩ ነው - ልቤ ሚሰማቸው።

በምን ተአምር ነው - ዛፎች የሚያረግዱት፣
በምን ጉድ አስማት ነው - የሰማይ ከዋክብት
ቁልቁል የሚበሩት።
እያልኩ አስባለሁ ….

እኔ ደግሞ ….
ቤሳ ቤስቲን ፍራንክ - ኪሴ ሳይጨመር፣
አመት የለበስኩት - ልብሴ ሳይቀየር።

የዘወትር ጉርሴ - ጣሙ ሳይነካ፣
እኔነት እኔ ውስጥ - ተቀይሯል ለካ።

እኮ በምን ምክንያት - እኔ ተቀየርኩኝ፣
እንዴት እኔ ነኝ ስል - እኔ ሌላ ሆንኩኝ።
እያልኩ አስባለሁ ……..
ለ ካ ስ ……………………..አፍቅሬሽ ነው!!!
#StayHome
#StaySafe